ጥቅምት 19 ቀን 2017 ዓም በኢትዮጵያ ቤተ-መዛግብትና ቤተ-መጻሕፍት አገልግሎት አዳራሽ ( ወመዘክር ) በተከናወነው “የአቦል አዳዲስ ይዘቶች ማስተዋወቂያና የአፋፍ ቴሌኖቬላ ማጠናቀቂያ” ልዩ ዝግጅት ላይ የተገኙት የባሕልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነፊሳ አልመህዲ " ዲኤስቲቪ በኢትዮጵያ የፊልም ጥበብ እንዲጎለብት በፋይናንስና በስርጭት እያደረገ ያለው አስተዋፅኦ ከፍተኛ ነው። በርካቶች የፊልም ጥበብ ባለሙያዎች ይህንን በመጠቀም እየተንቀሳቀሱ ነው" ሲሉ ተናግረዋል።

Nefisa Almahdi, State Minister for Culture and Sport. Credit: Supplied
በስኬት በመጠናቀቁም የይዘት ባለቤቱን ዲኤስቲቪ አቦል ቴሌቪዥንና አዘጋጁን ሚካኤል ሚሊዮንን ( ሰውኛ ፕሮዳክሽን ) እና አባላቱን እንኳን ደስ ያላችሁ ያሉ ሲሆን፤ ሚኒስትር ዴኤታዋ “ዲኤስቲቪ በስፖርቱ ነው የበለጠ የሚታወቀው ፣ በፊልምና መዝናኛ ይዘቶቹ እየሰራቸው ያሉ ስራዎችን እንደ ስፖርቱ ማስተዋወቅ ይጠበቅበታልም” ሲሉም አበረታተዋል።
የመልቲቾይዝ ( ዲኤስቲቪ ) ኢትዮጵያ የሬጉላቶሪና ኮርፖሬት ጉዳዮች ኃላፊ አቶ መታሰቢያ በላይነህ በበኩላቸው የኢትዮጵያን እሴትና ባሕል ጠብቀው የሚዘጋጁ ሀገርኛ የቴሌቪዥን ይዘቶች ከአቦል ቴሌቪዥን ስርጭት መጀመር በኋላ በጥራትና በብዛትም መበራከታቸውን ገልጸዋል።

Metasebya Belayneh, Head of Multi-choice (DSTV) Ethiopia Regulatory and Corporate Affairs. Credit: Supplied
መልቲቾይስ ለሀገርኛ ይዘቶች መጎልበትም አበክሮ ይሰራል ብለዋል። በመድረኩ የእሳት እራት፣ አሻራ፣ የልቤ፣ አላውቅም አናውቅም፣ እሹሩሩ፣ ምሕረት፣ ደማቆቹ፣ እንሞካከር፣ ስፍራሽ ብዙ፣ ሁለት ጓዳ፣ Ardaa Jilaa, Kiloolee እና Abbaa Karraa S3 ጨምሮ ሌሎችም እንዲተዋወቁ ተደርጓል።
በተወዳጅነት ለ281 ክፍሎች በሳምንት ለ5 ቀናት ሲተላለፍ የቆየው የአፋፍ ቴሌኖቬላ ሾው ራነር፣ ዳይሬክተርና ተዋናይ ሚካኤል ሚሊዮን በበኩሉ ዲኤስቲቪ በአቦል ቻናል ለኢትዮጵያ የፊልም ባለሙያዎች የፈጠረውን ዕድል አመስግኗል።

Actor Michael Million. Credit: Supplied
የአቦል አዳዲስ ተከታታይ ድራማዎች አዘጋጆች በመድረኩ ልምዳቸውንና የአቦልን አስተዋፅኦ ያጋሩ ሲሆን ይዘቶቻቸውንም አስተዋውቀዋል። አንተህ ኃይሌ ስለ “የእሳት እራት” ቴሌኖቬላ፣ ኑር አክመል ስለ “አሻራ” ቴሌኖቬላ፣ ፌቨን ከተማ ስለ “የልቤ” ድራማ እንዲሁም ኡስማን አወል ስለ ማዲ አቦል ይዘቶች ገለፃ አድርገዋል።
የተጠናቀቀው አፋፍ ቴሌኖቬላ አባላትም ስለ ትወና፣ ፕሮዳክሽን ማኔጅመንትና አጠቃላይ ይዘት ልምዳቸውን አጋርተዋል።
የዘንድሮ የጉማ አዋርድ የቴሌቪዥን ተከታታይ ምርጥ ተዋናይት ዘርፍ አሸናፊዋና የአፋፍ መሪ ገፀባሕሪይና ፕሮዲዩሰር መዐዛ ታከለ ( እስከዳር ) በዚሁ መድረክ ተመስግናለች።
በመድረኩ የተገኙት በኢትዮጵያ የሕንድ ኤምባሲ ም/ሰክረተሪ የሆኑት ሺሪ ራንጅት ኩማር ሕንድ ለኢትዮጵያ ፊልምና ባህል ዕድገት በተለያየ መልኩ ድጋፍ እያደረገች መሆኑን አስታውሰው በአቦል ቴሌቪዥን አማካኝነት እየተዘጋጀ ሲቀርብ ለነበረውና በሰውኛ ፕሮዳክሽን በላቀ ጥራት ለተሰራው አፋፍ ቴሌኖቬላ አድናቆታቸውን ገለፀዋል።

Credit: Supplied
ደማቅ ሆኖ በተጠናቀቀው በዚህ ልዩ ዝግጅት የታደሙት የአዲስ አበባ ባህል፣ ኪነጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ኃፍታይ ገ/እግዚአብሔር ዲኤስቲቪ /አቦል የኢትዮጵያ ፊልሞች እንዲዘጋጁና የላቀ ተደራሽነት እንዲኖራቸው እያደረገ ያለውን አስተዋፅኦ አድንቀዋል።
ሰውኛ ፕሮዳክሽንም የአፋፍ ቴሌኖቬላን የቀረፃ መንደር ገንብቶ ማዘጋጀቱ ለፊልም ኢንዱስትሪው ትልቅ ትምህርት ነው ያሉ ሲሆን መስሪያ ቤታቸውም ለዘርፉ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል።
መርሃግብሩ አስተዋፅኦ ላደረጉና በአፋፍ የዝግጅት ሂደት ለተሳተፉ ባለሙያዎች የዕውቅና የምስክር ወረቀት በመስጠት ተጠናቋል።