የፍትህ ሚኒስትሩ ዶክተር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ የሰላም ስምምነቱ ቀሪ ጉዳዮች ቢኖሩም ሽብርተኝነቱን ማንሳቱ በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ለማቋቋም እንደሚረዳ ተናግረዋል።
ምክር ቤቱ ፍረጃውን ያነሳው የፕሪቶሪያውን ስምምነት ተከትሎ ሲሆን፤ በስምምነቱ አንቀጽ 7/2 C መሰረት የፌዴራል መንግሥት በህወሓት ላይ የተጣለውን የሽብርተኝነት ስያሜ በምክር ቤቱ እንዲነሳ ሁኔታዎችን እንደሚያመቻች ተገልጿል።
ምክር ቤቱ ሚያዚያ 28 ቀን 2013 ዓ.ም ባካሄደው 6ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 13ኛ መደበኛ ስብሰባው ላይ ሕወሓትን አሸባሪ ብሎ መሰየሙ ይታወሳል።
የፌዴራል መንግሥትና ሕወሓት ጥቅምት 2015 ዓ.ም ላይ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ለ10 ቀናት ድርድር ካካሄዱ በኋላ የኢትዮጵያን የግዛት አንድነትና ጥቅም ባስከበረ መልኩ ስምምነት መፈጸማቸው ይታወቃል።
ፓርላማው ውሳኔውን በአብላጫ ድምፅ ያሳለፈው 61 የተቃውሞና አምስት ድምፀ ተዐቅቦ ገጥሞት ነው።