ለአውስትራሊያ ነባር ዜጎች ድምፅ ለፓርላማ ሕዝበ ውሳኔ ቀን ተቆረጠለት

የተባበሩት መንግሥታት ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን አማራ ክልል ውስጥ ተከስተው ባሉ ወታደራዊ ግጭቶች ሳቢያ ከወርኅ ጁላይ አንስቶ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ሕይወት መቀጠፉና እያሽቆለቆለ በመሔድ ያለው የሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ ያሳሰበው መሆኑን ገለጠ።

The Voice.jpg

Anthony Albanese has announced the date of the Voice to Parliament referendum. Credit: SBS

ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዚ "ማራቶን ለነባር ዜጎች፤ ለእኛ አጭር ርቅት" ብለው የጠሩት የአውስትራሊያ ነባር ዜጎች ድምፅ ለፓርላማ ሕዝበ ውሳኔ ቅዳሜ ኦክቶበር 14 / ጥቅምት 3 እንድሚካሔድ አስታወቁ።

አቶ አልባኒዚ በስድስት ሳምንታት ውስጥ እንዲካሔድ ቀን የቆረጡለትን ሕዝበ ውሳኔ ይፋ ያደርጉት ዛሬ ረቡዕ ነሐሴ 24 ከአደላይድ ከተማ ደቡብ አውስትራሊያ ነው።
Anthony Albanese.jpg
Anthony Albanese announced 14 October as the date when Australia's first referendum in a generation will be held. Credit: AAP / Mark Brake
ሕዝበ ውሳኔው ይሁንታ አግኝቶ በአብላጫ ድምፅ ካለፈ በተለይ የአውስትራሊያ ነባር ዜጎች ሕይወት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያሳድሩ ጉዳዮች ዕልባት እንዲበጅላቸው ምክረ ሃሳቦችን ለመንግሥት ሥራ አስፈፃሚና ለፓርላማ የሚያቀርብ ቋሚ አማካሪ አካል እንዲቋቋም ያስችላል።

የድምፅ ለፓርላማ አማካሪ አካሉ ምክረ ሃሳቦችን አቅራቢ እንጂ ውሳኔ ሰጪ ወይም ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ያለው አይደለም።

የድምፅ ለፓርላማ ደጋፊዎችና ተቃዋሚዎች የይሁንና አይሁን አተያይ ምንድን ናቸው?


የይሁን ካምፕ አተያዮች - ድምፅ ለፓርላማ

  • የአውስትራሊያ ነባር ዜጎችን በማድመጥ ስለ እነሱ ፖሊሲዎች ሲቀረፁ ውጤት አስገኚ እንዲሆኑ ያግዛል
  • ወደ ፊት ስልጣን ላይ የሚወጡ መንግሥታት እንዳይከሉት ሕገ መንግሥታዊ ጥበቃ ይኖረዋል
  • ነባር ዜጎች በኡሉሩ መግለጫ ከልብ አማካይነት ምን እንደሚሹ ያቀርቡት ጥያቄ ነው
የአይሁን ካምፕ አተያዮች - ድምፅ ለፓርላማ

  • አውስትራሊያውያንን በዘር ይከፋፍላል፤ ዘርን ሕገ መንግሥቱ ላይ ያክላል፣ የተለያየ የዜግነት መደቦችን ይፈጥራል
  • ሕጋዊ ተጋላጭነት ስላለው የሕግ ተግዳሮትን ይፈጥራል
  • በአውስትራሊያ ነባር ዜጎችና በተቀሩት አውስትራሊያን መካከል ያለውን ልዩነት አያጠብም፤ ዕርቅንም አያሰፍንም የሚሉ ናቸው።
ተመድ

የተባበሩት መንግሥታት ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ትናንት ነሐሴ 23 ባወጣው መግለጫ በአማራ ክልል በፌዴራል መንግሥቱና በአካባቢው ፋኖ ሚሊሺያ መካከል ተቀስቅሰው ባሉት ወታደራዊ ግጭቶች ሳቢያ የደረሱ የሕይወት ጥፋቶች እንዳሳሰቡት አመለክቷል።

የኮሚሽኑ ጽሕፈት ቤት ከሐምሌ 28 አንስቶ የተጣለውን አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተከትሎ ሁኔታዎች ተባብሰው የከፉ መሆኑንና 183 ያህል ሰዎች ሕይወታቸውን ያጡ መሆኑን አስታውቋል።

መግለጫው አክሎም፤ ከአንድ ሺህ በላይ ሰዎች በመላው ኢትዮጵያ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሕግ ተመርኩዞ ዘብጥያ መውረዳቸውንና በርካታ የአማራ ዝርያ ያላቸው ወጣቶች በፋኖ ደጋፊነት ተጠርጥረው ለእሥር መዳረጋቸውን የሚያመልክቱ ሪፖርቶች የደረሱት መሆኑን ገልጧል።

እርምጃዎቹን አስመልክቶም ባለ ስልጣናት ጅምላ እሥራትን እንዲገቱ፣ አልግባብ የታሠሩ እንዲለቀቁ፣ የተመድ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በሁሉም የዕገታ ሥፍራዎች መደበኛና ያልተገደበ ተደራሽነት እንዲኖራቸው እንዲደረግ ጥሪ አቅርቧል።

የተመድ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን አያይዞም፤ በፌዴራል ኃይሎች ጫና የፋኖ ሚሊሺያዎች ወደ ገጠራማ ሥፍራዎች ማምራት ጋር ተከትሎ ሁሉም ወገኖች ከግድያዎችና ሌሎች የአመፅ ድርጊቶች እንዲቆተቡ አሳስቦ፤ ቅሬታዎች በንግግርና ፖለቲካዊ ሂደቶች እንዲፈቱም አመላክቷል።

አክሎም፤ በአወዛጋቢው ምዕራባዊ ትግራይ 250 የትግራይ ዝርያ ያላቸው ግለሰቦች ታጣቂ የወልቃይት ወጣቶችን ጨምሮ፤ በአማራ ፖሊስና የአካባቢ ባለስልጣናት ለእገታ ተዳርገው እንደነበረና ከዚያም በመከላከያ ኃይሉ ስር እንደገቡ ታጋቾቹ ወደ ምዕራብ ትግራይ እንዲመለሱ ወይም በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ስር ወዳለው አካባቢ እንዲሆዱ አማራጭ የተሰጣቸው መሆኑን አንስቷል።

እንዲሁም፤ በኦሮሚያ ቀጥለው እንዳሉ የሚመለከቱት የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችም አሳስበውኛል ብሏል።

መግለጫው በማጠቃለያው፤ ሁሉም በተለያዩ ክልሎች የሚደርሱ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች በፍጥነት ገለተኛና ውጤታማ ምርመራ እንዲካሔድባቸውና ተጠያቂዎቹም ኃላፊነቱን እንዲወስዱ እንዲደረግ አሳስቧል።




Share
Published 30 August 2023 9:13pm
By Kassahun Seboqa Negewo
Source: SBS

Share this with family and friends