እንደራሴ ዳንኤል አንድሩስ የቪክቶሪያን 90 ፐርሰንት የኮሮናቫይረስ ገደቦች መውጫ ፍኖተ ካርታ ዛሬ ሐሙስ ኖቬምበር 18 ይፋ አደረጉ።
ቅዳሜ ኖቬምበር 20 ወይም 21 የቪክቶሪያ ተከታቢዎች ቁጥር 90 ፐርሰንት እንደሚደርስ በመገመቱ ተጥለው ያሉ የኮሮናቫይረስ ገደቦች ለሶስተኛ ጊዜ ዛሬ ከምሽቱ 11፡59pm ጀምሮ ይነሳሉ።
በዚህም መሠረት፤
ማኅበራዊ
- ቤትዎ ውስጥ በየቀኑ ያላንዳች የቁጥር ገደብ ጎብኚዎችዎን ማስተናገድ ይቻላሉ
- ከቤትዎ ውጪም በቡድን ያላንዳች የቁጥር ገደብ በቡድን ከሰዎች ጋር መሰባሰብ ይችላሉ (መናፈሻ ወም የባሕር ዳርቻ በመሳሰሉ ሥፍራዎች)
- ጎብኚዎችዎና በውጪ በቡድን የሚታደሟቸው ሰዎች ሙሉ ክትባት የተከተቡ እንዲሆኑ ይመከራል
የፊት ጭምብል
- ከቤትዎ ሲወጡ የፊት ጭምብል ለማድረግ ግድ አይሰኙም፤ ይሁንና የሰዎች እንቅስቃሴዎች በሚበረክቱባቸውና አካላዊ ርቀትን ለመጠበቅ በሚያስቸግሩ ሥፍራዎች የፊት ጭምብልን የማጥለቅ ግዴታ ባይኖርም ይመከራል።
- ከፍተኛ ተጋላጭነት ባለባቸው ሥፍራዎች እንደ ሆስፒታል፣ የአረጋውያን መከባከቢያ፣ የሕዝብ ትራንስፖርት፣ ፍርድ ቤትና የማረሚያ ተቋማትን በመሳሰሉ ሥፍራዎች የፊት ጭምብሎችን ማጥለቅ ግድ ይላል።
ቁሳቁሶችና አገልግሎቶች
- እንደ የችርቻሮ ሱቆችና ፓስታ ቤቶች የክትባት ማረጋገጫ አይጠየቅም
- የመፅሐፍ፣ የልብስ፣ አሻንጉሊቶች፣ ጌጣ ጌጥ መሸጫ የመሳሰሉ ሱቆችን ለመገልገል ሙሉ ክትባት መከተብን ግድ ይላል
- የፀጉር ማስተካከያ፣ የውበት ሳሎን፣ የሕዝብ ቤተ መፃሕፍት፣ የፈጠራ ስነ ስዕል መታያዎችን ግልጋሎት ለመጠቀም፣ የቤት ግዢ ጉብኝትና ጨረታዎች ላይ ለመገኘት ሙሉ ክትባት የተከተቡ ሊሆኑ ይገባል
መስተንግዶዎች
ሙሉ ክትባት የተከተቡ ከሆነ ሊስተናገዱ የሚችሉባቸው ሥፍራዎች (የክትባት መሥፈርቶችን የማያሟሉ ከሆነ መስተንግዶዎችን ማግኘት አይፈቀድልዎትም፤ የታዳሚዎች ቁጥር ገደብ የለም)
- የምግብና መጠጥ ሥፍራዎች (ምግብ ቤቶችና መጠጥ ቤቶችን የመሳሰሉ)
- የምሽት መዝናኛዎች (ቡና ቤቶችና ዳንስ ቤቶችን የመሳሰሉ)
- የመዝናኛ ሥፍራዎች (ሲኒማ ቤቶችና መካነ እንሰሳትን የመሳሰሉ)
- ኩነቶች (ፌስቲቫሎች፣ የመዝናኛ ሩጫዎችና ኮንፈረንሶችን የመሳሰሉ)
- ቱሪዝም (የእግርና አውቶቡስ ጉዞዎችን የመሳሰሉ)
- ካዚኖ/የቁማር መጫወቻና የጎልማሶች መዝናኛ ሥፍራዎችን የመሳሰሉ
መሥሪያ ቤቶች፣ ትምህርት ቤቶችና ሙዋዕለ ሕፃናት
- መሥሪያ ቤቶች ክፍት ይሆናሉ፤ የሚሠሩበት መሥሪያ ቤት ሙሉ ክትባት ለተከተቡ ብቻ ክፍት የሚሆን ከሆነ፣ በበጎ ፈቃደኝነት ወይም ከቤትዎ ውጪ የሚሠሩ ከሆነ ሙሉ ክትባት የተከተቡ ሊሆኑ ይገባል
- ትምህርት ቤቶች፣ የሕፃናት ክብካቤ ማዕከላትና ቅድመ ትምህርት ቤቶች በሁሉም ዕድሜ ላሉ ሁሉ ክፍት ይሆናሉ። የአንደኛ ደረጃ መምህራንና ሠራተኞች፣ ጎብኚዎችና ከሶስተኛ ክፍል በላይ ያሉ ተማሪዎች የፊት ጭምብል ሊያጠልቁ ይገባል
- ሙሉ ክትባት የተከተቡ ጎልማሳ ተማሪ ከሆኑ (ዩኒቨርሲቲና ኮሌጅ የመሳሳሰሉ) መማሪያ ክፍሎች ውስጥ ገብተው መማር ይችላሉ፤ ክትባት ያልተከተቡ ከሆነ ክፍሎች ውስጥ ገብተው መማር አይችሉም በኦንላይን ሊማሩ የማይችሉበት ሁኔታ ከሌለ በስተቀር
አካላዊ እንቅስቃሴ
- ሙሉ ክትባት የተከተቡ ካልሆነ የስፖርት እንቅስቃሴ ሥፍራዎችን (እንደ ስፖርት ሜዳዎች፣ የአካል ማጠንከሪያና የዋና ቦታዎች) የመሳሰሉትን መጠቀም አይችሉም
- የክትባት መመዘኛዎች የዋና ሥፍራን ለሕክምና የሚጠቀሙትን አይመለከትም
ጋብቻ፣ ቀብርና ቤተ እምነቶች
- ሁሉም ታዳሚዎች ሙሉ ክትባት የተከተቡ ከሆነ በሠርግ፣ የቀብርና የእምነት ሥነ ሥርዓቶች ላይ ያላንዳች የቁጥር ገደብና አካላዊ ርቀት መሥፈርት መታደም ይችላሉ
ቪክቶሪያ ውስጥ ባለፉት 24 ሰዓታት 1,007 ሰዎች በኮቪድ-19 ሲጠቁ 190 ፐርሰንት ሰዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል።